የትግራይ ክልል ተፈናቃዮች ከክረምቱ በፊት ሙሉ በሙሉ እንደሚመለሱ መንግሥት ገለጸ

Your browser doesn’t support HTML5

በአማራ እና በትግራይ ክልሎች አዋሳኞች የይገባኛል ጥያቄ ለሚነሣባቸው አካባቢዎች፣ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ዘላቂ እልባት ለመስጠት በብሔራዊ ደረጃ የተቋቋመው ኮሚቴ፣ ተፈናቃዮችን ወደ ቀዬአቸው ለመመለስ ቅድሚያ ሰጥቶ እንደሚሠራ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ አስታውቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ባለፈው ሳምንት ዐርብ፣ ከትግራይ ክልል የኅብረተሰብ ተወካዮች ጋራ ባደረጉት ውይይት፣ በአከራካሪ ቦታዎች ላይ የፌዴራሉ መንግሥት የጸጥታ ኀይሎች ብቻ እንደሚኖሩ ገልጸዋል። ከነዚኽ አካባቢዎች ተፈናቅለው በትግራይ ክልል የሚገኙ ተፈናቃዮች፣ በማንኛውም ሰዓት ወደ ቀዬአቸው ለመመለስ ከፈለጉ፣ መንግሥት ለማስፈጸም ዝግጁ እንደኾነም አበክረው ተናግረዋል።

ብሔራዊ ኮሚቴው፣ እስከ አሁን የተፈጸሙና ሊፈጸሙ ሲገባቸው የዘገዩ ጉዳዮችን መገምገሙን የዘገቡ መንግሥታዊ ብዙኀን መገናኛዎችም፣ ተፈናቃዮችን በአጭር ጊዜ ወደ ቀዬቸው ለመመለስ በሚቻልበት አግባብ ላይ ቅድሚያ ተሰጥቶት እንዲሠራ የጋራ መተማመን ላይ እንደተደረሰ አስታውቀዋል።