“የከለላ ጠያቂዎች ምዝገባ መቋረጥ አሳስቦኛል” ዩኤንኤችሲአር

Your browser doesn’t support HTML5

በኢትዮጵያ ከሦስት ዓመታት በላይ ለሆነ ጊዜ የተቋረጠው የከለላ ጠያቂዎች ምዝገባና ሰነድ የማግኘት ችግር እንዳሳሰበው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት፣ የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽነር /UNHCR/ አስታወቀ፡፡ ተቋሙ፣ የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት፣ የተቋረጠውን ምዝገባ እንዲያስጀምሩ ጠይቋል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን በበኩሉ፣ በሀገሪቱ የስደተኞችና ከለላ ጠያቂዎች ምዝገባ መቋረጥ፣ በነፃነት የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንደገደበ እና ሌሎችም ችግሮችን እያሰከተለ እንደሆነ፣ በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት አመልክቷል፡፡

ኮሚሽኑ፣ ባለፈው ሳምንት ያወጣው ሪፖርት በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙት ከ950 ሺህ በላይ ስደተኞች ለተለያዩ ችግሮች መጋለጣቸውን ያመለክታል፡፡ በኮሚሽኑ፣ የስደተኞች፣ የፍልሰተኞች እና የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች መብቶች ክፍል ዳይሬክተር እንጉዳይ መስቀሌ፣ ለአሜሪካ ድምፅ በሰጡት ማብራሪያ፣ በሪፖርቱ ከምዝገባ እና ሰነድ ከማግኘት ጋር ተያይዞ የሚነሳው ችግር፣ ትልቅ ትኩረት የሚሻ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የዚህ አገልግሎት ከሦስት ዓመታት በላይ መቋረጥ፣ ስደተኞችን እና ከለላ ጠያቂዎችን ለችግር እንደዳረጋቸውም አመልክተዋል፡፡