የላሊበላ አብያተ መቅደስ ታዛ በፍንጣሪ እንደተመታ እማኞች ተናገሩ

Your browser doesn’t support HTML5

የላሊበላ አብያተ መቅደስ ታዛ በፍንጣሪ እንደተመታ እማኞች ተናገሩ

በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን በላሊበላ ከተማና በአካባቢው በሃገር መከላከያ ኃይሉ እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ዛሬ (ረቡዕ) በከባድ መሣሪያ የታገዘ የተኩስ ልውውጥ መካሄዱን እማኝ ነን ያሉ ለቪኦኤ ተናግረዋል።

ከሦስት ሰዓት በላይ መዝለቁ በተገለፀው ረፋድ ላይ በተካሄደው የተኩስ ልውውጥ በህይወትና በአካል ላይ ጉዳት ደርሶ ከሆነና መጠኑንም እንደማያውቁ የላሊበላ ከተማ ነዋሪዎች አመልክተዋል።

በተኩስ ልውውጡ ወቅት ከውቅር አብያተ መቅደሱ በአንዱ ውስጥ ተጠልለው እንደነበር የተናገሩ አስተያየት ሰጭ በአካካቢው ተተኩሶ ነበር ያሉት ከባድ መሣሪያ ያስከተለው ፍንጣሪ አብያተ መቅደሱን ከዝናብ፣ ከፀሐይና ከነፋስ ጉዳት ለመከለል በተዘረጋው ታዛ ላይ ማረፉን ገልፀዋል።

አካባቢው በሰው ልጅ ሁሉ ካብትነት ተመዝግበው ዓለም አቀፍ እውቅናና እንክብካቤ የሚደረግላቸው ቅርሶች ያሉበት መሆኑን የተናገሩት ነዋሪዎች ሥፍራው ላይ የከባድ መሣሪያ ልውውጥ ስለማስተዋላቸው እማኝነት ሰጥተዋል።

እንዲሁም ደቡብ ወሎ ዞን አምባሰል ወረዳ ወረዳ ውስጥ በሚገኘው ውጫሌ ከተማ ባለፈው ሣምንት ቅዳሜና ዕሁድ በመግሥቱ ኃይሎችና በአማፂያኑ ፋኖ መካከል በተካሄደ ግጭት አንድ ሲቪል መገደሉን፣ አንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ቢሮ መቃጠሉንና በተቋማቱ ውስጥ የነበሩ ኮምፕዩተሮች ጉዳት እንደደረሰባቸው ነዋሪዎች ለቪኦኤ ገልፀዋል።

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ያገኛሉ።