ሩሲያ ወታደራዊ ስልጠና በት/ቤቶች ልትሰጥ ነው

  • ቪኦኤ ዜና

የሩሲያ ጦር አባል በልምምድ ላይ

የእንግሊዝ መከላከያ ሚኒስቴር በዩክሬን ላይ በሚያወጣው ዕለታዊ የወታደራዊ መረጃ መግልጫ ላይ ዛሬ እንዳስታወቀው፣ ከሚቀጥለው ዓመት መስከረም ወር ጀምሮ በሩሲያ ወታደራዊ ስልጠና በት/ቤቶች ተመልሶ እንደሚሠጥ የሃገሪቱ የትምህርት ሚኒስትር ተናግረዋል።

ከስልጠናው ውስጥ የኬሚካልና የኑክሌር ጥቃት ቢፈጸም ስለሚኖር ጥንቃቄ፣ የመጀመሪያ ርዳታ እና ስለ ካላሺንኮቭ ጠመንጃ አጠቃቀም ይገኙበታል።

ሪፖርቱ እንዳለው ሩሲያ በአሁኑ ወቅት የሥረዓተ-ትምህርቱን በማርቀቅ ላይ ስትሆን፣ በአመቱ መጨረሻ ተጠናቆ የማጽደቅ ሂደቱ ይጀመራል።

የዩክሬኑ ፕሬዝደንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ትናንት በምሽታዊ የቪዲዮ መልዕክታቸው፣ በኬርሶን ሠራዊታቸው የተቀዳጀውን ድል አድንቀዋል።

ሠራዊታቸው በኬርሶን ክልል 60 አካባቢዎችን እንዳስለቀቀ ተናግረዋል።

ዜሌንስኪ ከምሥራች ዜናው ጋር ማስጠንቀቂያም አክለዋል፤ በኬርሶን ያሉ ሰዎች ደስታ ላይ ቢሆኑም፣ በዶንስክ ግን በየቀኑ ዘግናኝ ውጊያ እየተደረገ ነው ብለዋል።

“እዛ ያለው ሁኔታ ገሃነም ነው” ሲሉ ተደምጠዋል።