የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን መግለጫ አና የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ምላሽ

Your browser doesn’t support HTML5

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በኢትዮጵያ ሁኔታ ላይ በአስቸኳይ በመምከር እርምጃ እንዲወስድ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ባለሞያዎች ኮሚሽን ጠየቀ።

በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ለመመርመር የተቋቋመው ኮሚሽን፣ የፀጥታው ምክር ቤት የኢትዮጵያን ጉዳይ ዋና አጀንዳው አድርጎ ለመቀጠል የደረሰበትን ውሳኔ እደግፋለሁ ብሏል።

ለዚህ የዓለምአቀፉ የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን መግለጫ የኢትዮጵያ መንግሥት በሰጠው ምላሽ፣ የኮሚሽኑ መግለጫ እንዳሳዘነው እና እንደማይቀበለውም አስታውቋል፡፡

“ኮሚሽኑ ሰብአዊ መብቶችን ለፖለቲካዊ ጫና በመሳሪያነት በመጠቀም እውነተኛ አላማውን አጋልጧል” ያለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ “በዚህም ከመንግሥት ጋር ያለውን የትብብር በሮች በሙሉ ዘግቷል” ሲል አቋሙን አንፀባርቋል።

ኤርትራም የኮሚሽኑን መግለጫ ያወገዘች ሲሆን፣ ከህወሓት ወገን ግን እስካሁን የተሰጠ ምላሽ የለም፡፡

በሌላ ዜና፣ ህወሓት በሰሜን ኢትዮጵያ የሚካሄደውን ለማቆም አራት ቅድመ ሁኔታዎችን አቅርቧል፡፡ በትግራይ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ማስጀመር እና ጦርነቱ በጥቅምት 2013 ዓ.ም ከመጀመሩ በፊት የነበረውን የትግራይ ወሰን ማክበር ከቅድመ ሁኔታዎቹ መካከል ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ እንደማይቀበል የገለጸው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ ለአሁኑ ጥያቄ እስካሁን ምላሽ አልሰጠም፡፡