በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ሩስያ የኒውክሌር መሳሪያ ወደ ሕዋ የመላክን ሃሳብ የሚያግደውን የመንግስታቱ ድርጅት ውሳኔ ውድቅ አደረገች


ፎቶ ፋይል፦ በተባበሩት መንግስታት የሩስያ አምባሳደር ቫሲሊ ኔቤንዚያ
ፎቶ ፋይል፦ በተባበሩት መንግስታት የሩስያ አምባሳደር ቫሲሊ ኔቤንዚያ

ሩስያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አገሮች በሕዋ ላይ የሚያደርጉትን የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እሽቅድድም ለመከልከል በትላንትናው ዕለት ያሳለፈውን ውሳኔ በመቃወም ድምጽን በድምጽ የመሻር መብቷን ለመጠቀም የወሰደችውን እርምጃ ተከላከለች። ‘ሁሉም ዓይነት የጦር መሳሪያዎች፣ ሁልጊዜም ነው መታገድ ያለባቸው’ ስትልም በልዋጩ ያቀረበችውን ሃሳብ እንዲደግፉት ዩናይትድ ስቴትስን፣ ጃፓንን እና ምዕራባውያን አጋሮቻቸውን የሞገተ ጥሪ አሰምታለች።

ውድቅ የተደረገውን ውሳኔ የደገፉትን ዩናይትድ ስቴትስን እና ጃፓንን ‘በግብዝነት’ የተቹት በተባበሩት መንግስታት የሩስያ አምባሳደር ቫሲሊ ኔቤንዚያ ‘ለእነርሱ ብቻ ሲሆን የሚሰራ አቀራረብ ነው’ ሲሉ ነቅፈዋል።” በተለይም “የተቀነባበሩ ወታደራዊ የውጊያ መሳሪያዎችን” ማሰማራትን ጨምሮ በሕዋ ላይ የሚፈጸም ወታደራዊ አሰሳ የማድረግ እቅድ ይዘዋል’ ሲሉ ዩናይትድ ስቴትስን እና ምዕራባውያን ሃገራትን ወንጅለዋል።

“እውነታው ሩስያ በአሁኑ ወቅት በርካታ መደበኛ ፀረ-ሳተላይት የጦር መሳሪያዎች ምህዋር ያላት መሆኑ ነው” ሲሉ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ የተናገሩት የዩናይትድ ስቴትሱ ምክትል አምባሳደር ሮበርት ውድ በበኩላቸው ‘ከእነዚህም ውስጥ አንዱ በ2019 የሞከረችው ነው” ብለዋል። አክለውም ሩስያ ሳተላይቶችን የጦር መሳሪያዋ ኢላማ ለማድረግ ዝታለች፣ "አዲስ ሳተላይት ተሸካሚ የኒውክሌር መሳሪያ እየሰራች መሆኗን የሚያሳይ አስተማማኝ መረጃም አለ" ብለዋል።

የቃላት ልውውጡ የተሰማው ሩስያ የእንግሊዝን ወታደራዊ ተቋማት ዒላማ እንደምታደርግ እና ታክቲካዊ የውጊያ የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎችን በምሥል የሚገለገል የጦር ልምምድ ለማድረግ ማቀዷን በተናገረችበት ዕለት ነው። ሞስኮ የተባለውን ዛቻ ያሰማችው ምዕራባውያን ከፍተኛ ባለስልጣናት በዩክሬኑ ጦርነት ጠለቅ ያለ ሚና መኖር መቻሉን አስመልክቶ ለሰጡት አስተያየት ምላሽ ነበር።

የመንግስታቱ ድርጅት የሩስያን ታክቲካዊ የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎችን አስመስሎ መጠቀም የሚጨምር የጦር ልምምድ ዕቅድ መሰማት ተከትሎ የተለያዩ ወገኖች ሰሞኑን በኒውክሌር ጦር መሳሪያዎች ዙሪያ የሚደረጉት ንግግሮች ስለከሰተው እና እያየለ ስለመጣው ስጋት አስጠንቅቋል።

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG