በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የኢሉባቦር አሌ ወረዳ ነዋሪዎች ከጉመሮ ሻይ ፋብሪካ በቂ ጥቅም አናገኝም ሲሉ ቅሬታቸዉን አሰሙ


በኢሉባቦርአሌ ወረዳ ጉመሮ ሻይ ፋብሪካ /ፋይል ፎቶ/
በኢሉባቦርአሌ ወረዳ ጉመሮ ሻይ ፋብሪካ /ፋይል ፎቶ/

የኢሉባቦር አሌ ወረዳ ነዋሪዎች፥ በወረዳቸዉ ከሚገኘዉ ከጉመሮ ሻይ ፋብሪካ፥ በቂ ጥቅም እያገኘን አይደለም ሲሉ ቅሬታቸዉን ለአሜርካ ድምጽ አሰሙ። ነዋሪዎቹ በተለይፋብሪካዉ የሰዉ ኃይል ሲቀጥር በቂ ዕድል ለአካባቢዉ ነዋሪዎች አይሰጥም ብለዉ አቤቱታ ሲያሰሙ፥ ፋብሪካዉ ግን የነዋሪዎቹን ጥቅም ለማስጠበቅ እየሰራሁ ነኝ ሲል መልስሰጥቷል።

በጉመሮ ሻይ ፋብሪካ ዙሪያ የሚኖሩ የአሌ ወረዳ ነዋሪዎች ከፋብሪካዉ የሚገባንን ጥቅም እያገኘን አይደለንም በማለት ያላቸዉን ቅሬታ አሰምተዋል።

ስማቸዉ እንዳይገለጽ የፈለጉ በፋብሪካዉ ዙርያ የሚኖሩ ነዋሪዎች እንደሚሉት፥ ፋብሪካዉ መጀመሪያ ሲቋቋም ከአካባቢዉ እንዲነሱ የተደረጉ አርሶ አደሮች፥ ለመሬታቸዉ ምንም ካሳ አልተከፈላቸውም።

ከዚህም በተጨማሪ ፋብሪካዉ ሠራተኛ ሲቀጥር ለእኛ የአካባቢዉ ነዋሪዎች በቂ ዕድል አይሰጥም በማለት ቅሬታ እንዳላቸዉ ይገልጻሉ። ”ፋብሪካዉ መጀመርያ ሲቋቋም ከቦታዉ ለተነሱ አርሶ አደሮች በቂ ካሳ ሳይሰጧቸዉ ነዉ ከመሬታቸዉ ያነሷቸዉ። በሌላ በኩል ደግሞ የተማሩ የአካባቢዉ ወጣቶችበፋብሪካዉ ተቀጥረው ሲሰሩ፥ ለቦታው ተመጣጣኝ ደሞዝ እያገኙ አይከፈሉም። እኚህ የአካባቢዉ ወጣቶች እያሉ ከደቡብ አልያም ከሰሜን ነዉ አምጥተዉ የሚቀጥሩት።” ብለዋል።

ሌላ የአባቢዉ ወጣት ሲናገር በተለይ የአካባቢዉ አርሶ አደሮች ላሞችና ፍየሎች በፋብሪካዉ መሬት ክልል ዉስጥ ሲገኙ ፋብሪካዉ ከባድ ቅጣት ይቀጣል። በዚህም የተነሳ ቤተሰቤ ከቦታዉ ለቋል ሲል ይናገራል።

በቅርቡም በፋብሪካዉ ማሳ ላይ የእሳት ቃጠሎ ደርሶ ነበር። ህዝቡ ባደረገዉ ስብሰባ ላይ ቅሬታ ቢያቀርብም፥ ፋብሪካዉ ግን በቂ መልስ ሳይሰጠን እንዲሁ በቸልተኝነት አለፈ ሲል ይህ ወጣቱ ገልጿል። ”እኔና ቤተ ሰቦቼ እዚሁ ፋብሪካዉ ዙርያ ነበር የምንኖረው። የሚንከፍለዉ ቅጣት ሲከብደን ቦታዉን ለቀቅን። ከብቶች፣ ፍየሎች፣ በጎችና አህዮች ወደ ፋብሪካዉ ማሳ ከገቡየሚጣለዉ ቅጣት በጣም ከፍተኛ ነዉ። ቢያንስ ለአንድ አህያ ወደ 150 ብር ነዉ የምንከፍለዉ። ባለፈዉ ጊዜ በፋብሪካዉ ማሳ ላይ ባልታወቀ ሁኔታ የእሳት አደጋ ደርሶ ነበር።በዚያ የተነሳ በተደረገዉ ስብሰባ ላይ የአካባቢዉ አርሶ አደሮች ለወረዳዉ አስዳደርና ለፋብሪካዉ ቅሬታ ቢያቀርቡም፥ በስብሰባዉ ላይ የነበሩ የፋብሪካዉ ተወካይ ግን፥ እኛን የሚያስተዳድረን የፌደራል መንግስት እንጂ የወረዳው አስተዳደር አይደለም ሲሉ ነዉ መልስ የሰጡን። በጊዜዉ ጥያቄ ያቀረቡትን ሰዎችንም የደሞዝ ቅጣትና የተለያዩ እርምጃ ነዉየወሰዱባቸዉ።” ብሏል ወጣቱ።

የነዋሪዎቹን ቅሬታ አስመልክተን የፋብሪካዉን ዋና ሥራ አስከያጅ አቶ መሠረት ጥሩነህ ተሰማን የጠየቅን ሲሆን እሳቸዉ እንደሚሉት ግን የቀረበዉ አቤቱታ የተጋነነ ነዉ።የአካባቢዉ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በተቻለን መጠን በመሥራት ላይ ነን ሲሉ አስረድተዋል።።

”ምንድነዉ አሁን እዚህ ጋር ከብቶች አሉ፥ አህዮች አሉ። እነዚህ ከብቶችና አህዮች በቀጥታ በልማቱ ክልል ዉስጥ ገብተዉ አይደለም መሰማራት ያለባቸዉ። ሆኖም እኛ ገንዘብ አስከፍለን ልማትን ትርፋማ ለማድረግ አይደለም። ይሄ፣ አሁን ልማቱ ዉስጥ ደን አለ (RESERVED) የሆነ ደን ስለዚህ ገበሬዎች ከብቶቻቸዉን ማሰማራት ያለባቸዉ እዚህ ደን ዉስጥ ነዉ። እንደገና ሻይ ተክል ዉስጥም ከብቶች ይሰማራሉ። ሻይ ደግሞ በተፈጥሮዉ ከዬትኛዉም እንስሳ ጋራ ንክኪ እንዲኖረዉ አይፈቀድም። ምክንያቱም ከጥራቱ ጋር ተያይዞነዉ። የ Rain Forest Alliance Certification ይከለክላል። ስለዚህ ከብቶቻችሁን ጠብቁ፣ ፈረሶቻችሁንም አህዮቻችሁንም ጠብቁ ብለን ማስታወቅያ ሁሉ እየለጠፍን ነዉየምንነግረዉ። ይሄን ሁሉ አድርገን እምቢ ሲሉ ምናልባት በአንድ ከብት እስከ 25 ብር እነዲቀጡ ይደረጋል።” ብለዋል።

በሰዉ ኃይል ቅጥር ዙርያ የነዋሪዎቹን ስሞታ ግን ሥራ አስከያጁ አስተባብለዋል። በቅርቡ በፋብሪካዉ ማሳ ላይ ደርሶ ነበር የተባለዉ የእሳት አደጋም ማናልባት እየተነሳ ካለዉየህዝብ ቅሬታ ጋር ይያያዛል ወይ ብለን የወረዳዉን ምክትል አስተዳደር አቶ ወራቃ አያናን ስንጠይቅ፥ ጉዳዩ እስካሁን በፖሊስ እጅ ነዉ ብለዋል። ወደፊት የአካባቢዉ ወጣቶችበፋብሪካዉ ዉስጥ ተቀጥረዉ በይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ወረዳዉ ከፋብሪካዉ ጋር እየሰራ መሆኑንም አክለው ተናግረዋል።

የጉመሮ ሻይ ልማት ድርጅት በሚድሮክ ኢትዮጵያ የሚተዳደር የግል የሻይ ፋብሪካ ሲሆን፥ በዊኪሊክስ የተለቀቀዉ መረጃ እንደሚያመለክተዉ ሚድሮክ ኢትዮጵያ ግሩፕ በ 24ሚሊዮን ዶላር ነዉ ከኢትዮጵያ መንግስት የገዛዉ።

ገልሞ ዳዊት ከናይሮቢ ያጠናቀረው ዘገባ ዝርዝሩን ይዟል፣ ከድምጽ ፋይልይ ያድምጡ።

የኢሉባቦር አሌ ወረዳ ነዋሪዎች ከጉመሮ ሻይ ፋብሪካ በቂ ጥቅም አናገኝም ሲሉ ቅሬታቸዉን አሰሙ
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:20 0:00
ቀጥተኛ መገናኛ

XS
SM
MD
LG