በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ሕዝባዊ ውይይቶች ይበልጥ አሳታፊ እንዲሆኑ የኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ጠየቁ


ሕዝባዊ ውይይቶች ይበልጥ አሳታፊ እንዲሆኑ የኦሮሚያ ክልል ነዋሪዎች ጠየቁ
please wait

No media source currently available

0:00 0:05:35 0:00

በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች ከፌደራል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የክልል ርእሳነ መስተዳድሮች ጋራ በወቅታዊ የጸጥታ ችግሮች ላይ ከትላንት በስቲያ ቅዳሜ የተወያዩ ነዋሪዎች፣ ሕዝባዊ ውይይቶቹ ይበልጥ አሳታፊ እንዲሆኑ ጠይቀዋል፡፡

የአሜሪካ ድምፅ ያነጋገራቸው የስብሰባው ተሳታፊዎች እና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች፣ ሕዝባዊ ውይይት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፣ ኾኖም ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች እና የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ቢሳተፉ የተሻለ እንደሚሆን ተናግረዋል።

በአገሪቱ ያለው ችግር በግልጽ እንደሚታወቅ አስተያየት ሰጭዎቹ ጠቅሰው፣ ከኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ጋራ የተጀመረው ድርድር ቢቀጥል ውጤት ሊኖር ይችላል፤ ብለዋል፡፡

ውይይቱን የመሩት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣት በበኩላቸው፣ በኦሮሚያ ክልል እየተስተዋለ ያለውን ችግር መረዳታቸውን ገልጸው፣ ለመፍትሔዎቹም እንደሚሠሩ ቃል ገብተዋል።

በክልሉ የተለያዩ ከተሞች ከተካሔዱት መድረኮች መካከል፣ በአዳማ ከተማ የተካሔደውን ውይይት የመሩት የኦሮሚያ ክልል ርእሰ መስተዳድር እና የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሽመልስ አብዲሳ፣ ጥያቄዎችን በሰላማዊ መንገድ ለመመለስ መንግሥት ዝግጁ ነው፤ ማለታቸውን የመንግሥት ብዙኀን መገናኛዎች ዘግበዋል።

በአምቦ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የኾኑት ሰሎሞን ተፈራ፣ መንግሥት ሕዝባዊ ውይይቶችን ማመቻቸቱ ከታጣቂዎች ጋራ ለሚደረገው የሰላም ድርድር አስተዋፅኦ እንዳለው፣ ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።

ዝርዝሩን ከተያያዘው ፋይል ያዳምጡ።

XS
SM
MD
LG