በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ሞርሲ ተነሱ፣ ሕገመንግሥቱ ተቋረጠ


ሞሐመድ ሞርሲ
ሞሐመድ ሞርሲ

ሕገመንግሥቱን ማቋረጣቸውንና ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲን ከሥልጣናቸው ማስወገዳቸውን የግብፅ ወታደራዊ አዛዥ አስታወቁ፡፡




የግብፅ ጦር ኃይሎች አዛዥ ጄነራል አብዱልፋታህ ኻሊል አል-ሲሲ
የግብፅ ጦር ኃይሎች አዛዥ ጄነራል አብዱልፋታህ ኻሊል አል-ሲሲ


በጣሕሪር አደባባይ የተሰበሰቡ ተቃዋሚዎች ደስታቸውን በከፍተኛ ድምፅ እና ርችት እየተኮሱ እየገለፁ ናቸው
በጣሕሪር አደባባይ የተሰበሰቡ ተቃዋሚዎች ደስታቸውን በከፍተኛ ድምፅ እና ርችት እየተኮሱ እየገለፁ ናቸው
ሕገመንግሥቱን ማቋረጣቸውንና ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲን ከሥልጣናቸው ማስወገዳቸውን የግብፅ ወታደራዊ አዛዥ አስታወቁ፡፡

please wait

No media source currently available

0:00 0:05:10 0:00
ቀጥተኛ መገናኛ

የሃገሪቱ የጦር ኃይሎች አዛዥ ጄነራል አብዱልፋታህ ኻሊል አል-ሲሲ ከተቃዋሚዎች ተወካዮች እና ከሐይማኖት መሪዎች ጋር ሆነው በሰጡት መግለጫ ሕገመንግሥቱን በጊዜያዊነት ማቋረጣቸውን ተናግረዋል፡፡

የፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲ ድምፅ ነው ተብሎ በናስር መንደር ለተሰበሰበ ደጋፊያቸው በተሰማው መልዕክት ፕሬዚዳንቱ በወታደሮቹ የተወሰደውን እርምጃ ሙሉ በሙሉ እንደሚያወግዙ አስታውቀዋል፡፡ “ግብፅ ያላት ሕጋዊ ፕሬዚዳንት አንድ ነው፤ እርሱም ሞሐመድ ሞርሲ ብቻ ነው” ያሉት በጦር ኃይሎቹ መነሣታቸው የተገለፀው ሞርሲ “በጥር 25ቱ አብዮት የወደቁ ልጆች ደም እንዳይባክን ግብፃዊያን በመፈንቅለ መንግሥቱ መንገድ ላይ እንዲቆሙ” ጥሪ አሰምተዋል፡፡

ተከታዩ መንግሥት በምርጫ እስኪሰየም ድረስ የሕገመንግሥታዊው ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ አድሊ ማንሱር የሃገሪቱን የመንግሥት ሥራ አስፈፃሚ ሥራዎች እንደሚያከናውኑ ጄነራል ሲሲ አስታውቀዋል፡፡

የሽግግሩ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ በወታደራዊው ዕቅድ የተሰየሙት የሕገ መንግሥታዊው ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ አድሊ ማንሱር ባሰሙት ንግግር ደም መፋሰስን ለማስወገድ እንደሚጥሩ አስታውቀዋል፡፡ የአሁንን እርምጃ ያመጣው “ያለፈው መንግሥት” ለዕርቅ መሥራት ስለተሣነው መሆኑን የጠቆሙት አዲሱ ፕሬዚዳንት እርሣቸው ለዕርቅ እንደሚጥሩ ቃል ገብተዋል፡፡

የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎችና ወጣቶች በፖለቲካው ሂደት ውስጥ እንዲሣተፉ እንደሚያበረታቱ አዛዡ አስታውቀዋል፡፡

በጣሕሪር አደባባይ የተሰበሰቡ ተቃዋሚዎች ደስታቸውን በከፍተኛ ድምፅ እና ርችት እየተኮሱ እየገለፁ ሲሆን የሙስሊም ወንድማማችነት መሪዎች ቀደም ሲል በሰጡት መግለጫ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደ ነፃ ምርጫ የተመረጡ ፕሬዚዳንታቸውን ለመጠበቅ እንደሚፋለሙ ሲዝቱ እንደነበር ይታወቃል፡፡

የፕሬዚዳንቱ ፅሕፈት ቤት በትዊተር ገፁ ላይ ባወጣው መልዕክት “ስለ ግብፅ እና ለታሪክም ትክክለኛነት ስንል እየተካሄደ ያለውን በስሙ እንጥራውና ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ነው” ብሎታል፡፡ ሞርሲ በዚያው የፕሬዚዳንቱ የትዊተር ገፅ ላይ ዘግየት ብለው ባወጡት ሌላ መልዕክት “በጦር ኃይሎቹ መሪዎች የተወሰዱት እርምጃዎች የሚያሣዩት በሃገራችን ነፃ ሰዎች ሁሉ የተወገዘ ሙሉ መፈንቅለ-መንግሥት መካሄዱን ነው” ብለዋል፡፡

የአል አዝሃር መስጂድ ዋና ኢማም ሼኽ አሕመድ አል ጠይብና የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ሊቀ-ጳጳስ አቡነ ቴዎድሮስ ዳግማዊ በየተራ ባደረጉት ንግግር አምላክ ግብፅንና ሕዝቧን እንዲጠብቅ ለምነዋል፡፡

የተቃዋሚዎቹ ተጠሪ ሞሐመድ አል ባራዳይ ባሰሙት ንግግር የጦር ኃይሎቹ ያቀረቡት ዕቅድ “የግብፅ አብዮት ባለፈው ዓመት የተነሣሣለትን ማኅበራዊ ፍትሕ እና ነፃነት ለማስገኘት የመንደርደሪያ ደንጊያ ነው” ብለውታል፡፡ አልባራዳይ አክለውም ይህ ዕቅድ “የአብዮቱ መንገድ ማስተካከያ እርምጃ ነው”ም ሲሉ ጠርተውታል፡፡

ዕቅዱ ከሚያካትታቸው ቁልፍ ካሏቸው ተግባራት መካከልም “ከጊዜው በፊት ፈጥኖ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማካሄድ፣ ሕገመንግሥታዊ ማሻሻያ ማድረግ፣ በሚሰየም የዕርቅ ኮሚሽን ብሔራዊ ዕርቅ መፍጠር” እንደሚገኙበት ዘርዝረዋል፡፡

የታማሩድ የወጣቶች ንቅናቄ መሪ ባሰማው ንግግር እርምጃው በግብፅ ታሪክ ውስጥ አዲስ ክንዋኔ መሆኑን ጠቁሞ “ግብፅ መገፋት የሌለባት፣ ለክብራቸው፣ ለነፃነትና ለማኅበራዊ ፍትሕ እምቢ ባይ የሆኑት የሁሉም ግብፃዊያን የሆነች ሃገር ነች” ብሏል፡፡

በጊዛው ካይሮ ዩኒቨርሰቲ ትናንት በተካሄዱ ግጭቶች የ18 ሰው ሕይወት መጥፋቱ ተገልጿል፡፡

ጄነራል ሲሲ የሃገሪቱ መፃዒ ዕጣ ፈንታ ዕቅድ ያሉትን ካነበቡና የፕሬዚዳንቱን መወገድ ካስታወቁ ወዲህ የተፈጠረ ግጭት ይኑር ወይም አይኑር ለጊዜው በግልፅ የወጣ ዘገባ የለም፡፡

ወታደሮች ካይሮ የሚገኘውን የአል-ጃዚራ የዜና አውታር የቴሌቪዥን ቻናልና ሌሎች ሦስት የሙስሊም ወንድማማችነት ፓርቲ ዘመም የሆኑ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን መውረራቸውና መዝጋታቸው ተሰምቷል፡፡

የግብፅን ሁኔታ ዋይት ሃውስ በቅርብ እየተከታተለው ሲሆን ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከመከላከያ ሚኒስቴርና የስለላ ተቋሙ - ሲአይኤ ኃላፊዎች ጋር ለአስቸኳይ ስብሰባ ተቀምጠው ከመከሩ በኋላ የግብፅ ሁኔታ በእጅጉ እያሳሰባቸው መሆኑን የሚናገር መግለጫ አውጥተዋል፡፡

ፕሬዚዳንት ኦባማ አክለውም ግብፅ ፈጥና ወደ ሲቪል አስተዳደር እንድትመለስ አሳስበው ወገኖች ሁሉ መቻቻልን እንዲያሣዩ ጠይቀዋል፡፡

ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ሞርሲ እና ሌሎች የሙስሊም ወንድማማችነት መሪዎች መታሠራቸውን የሚጠቁሙ ዘገባዎች በቅርቡ እየወጡ ነው፡፡
XS
SM
MD
LG