ዋሺንግተን ዲሲ - አዲስ አበባ —
የኅዳሴ ግድብን የቴክኒክ ጥናት ሂደት እንዲመራ የተሰየመው የኢትዮጵያ፣ የሱዳንና የግብፅ የጋራ ኮሚቴ ዛሬና ነገን (ረቡዕና ሐሙስ) ለሚዘልቅ ስብሰባ አዲስ አበባ ላይ ተቀምጧል፡፡
ኮሚቴው በዚህ አምስተኛ ስብሰባው ወቅት የቴክኒክ ጥናቱን የሚያካሂድ ዓለምአቀፍ ድርጅት ይመርጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በስብሰባው ላይ የሦስቱ ሃገሮች የውኃ፣ ኢነርጂና መስኖ ጉዳዮች ሚኒስትሮች፣ ኤክስፐርቶች፣ የዲፕሎማሲ ባለሙያዎችና ሌሎችም እየተሣተፉ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የድርጅቱ ምርጫ የሚካሄደው ቀደም ሲል በመጣ አጭር ዝርዝር ላይ ከቀሩ አራት አማካሪ ኩባንያዎች መካከል መሆኑንና መራጮቹ የሚመለከቱት የቴክኒክና የበጀት ሰነዶችን እንደሚሆን የምሥራቅ ናይል ተፋሰስ ዞን ፅ/ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈቅአሕመድ ነጋሽ ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡
ከአቶ ፈቅአሕመድ ነጋሽ ጋር የተደረገውን ሙሉ ቃለ-ልምምስ ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡