የአዲስ አበባ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኰሌጅ ተማሪዎች ትምህርት ካቆሙ ከሁለት ሣምንት በኋላ ዛሬ ወደ ትምህርት ገበታቸው መመለሳቸውን ለስድስት ቀናት ያካሄዱትን የረሀብ ዓድማም ማቆማቸውን ተማሪዎቹ እራሣቸው ገልፀዋል።
አዲሱ አበበ አንድ በስም መጠቀስ ያልፈለገ ተማሪና፣ በሽምግልናው የተሣተፉ አንድ አባት አነጋግሯል፡፡
በቀደመ ዘገባችን ተማሪዎቹ ትምህርት ካቆሙ 14ኛ ቀናቸው ላይ መሆናቸውን፣ በረሀብ ዓድማው ምክንያት ተዳክመው ሐኪም ቤት የገቡ መኖራቸውን፣ የታሠረ አንድ ተማሪም ገና ትናንት መፈታቱን መናገራችን ይታወሳል።
በዚሁ ዘገባች ግን ፓትርያርኩ ይቋቋማል ያሉት ኰሚቴ ለምን እንዳልተቋቋመ ጠይቀን «እየተማሩ ጉዳዩን እናየዋለን ብዬ መክሬያቸው ነበርና ትምህርታቸውን ስላልጀመሩ ነው፤ አሁንም ኮሚቴው ሥራውን ይጀምራል፤ እነርሱም ትምህርት መጀመር አለባቸው» ባሉት መሠረት ይመስላል ተማሪዎቹ ዛሬ ወደ ትምህርት ገበታቸው የተመለሱት።
ትናንት ፓትርያርኩ የሰጡትን ገለፃም ከተያያዘው ዘገባ ያዳምጡ። አዲሱ ዛሬ ካነጋገረው ተማሪ ገለፃ እንነሳለን።