በኤርትራ ላይ እርምጃ ሊወስዱ እንደሚችሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ ዛቱ፡፡
የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያንና ጎረቤት ሃገሮችን የማተራመስ ስትራተጂውን ካልቀየረ እርምጃ የምንወስድበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል ብለዋል ጠቅላይ የሚኒስትሩ ዛሬ ለፓርላማቸው ባደረጉት ንግግር፡፡
ጊዜው ሲደርስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ገልፀን አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ የምንገደድበት ሁኔታ ይኖራል ሲሉ አቶ ኃይለማርያም አስጠንቅቀዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የ2007ቱ ብሔራዊ ምርጫ ዲሞክራሲያዊ፥ ፍትሐዊና ሰላማዊ ነው ብለዋል የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር በዚሁ የዛሬ የፓርላማ ንግግራቸው፡፡
“ሌሎች ምን አሉ?” የሚለው ብዙም እንደማያሳስባቸው ያመለከቱት አቶ ኃይለማሪያም ገዥው ፓርቲና መንግሥት በህጋዊና በሠላማዊ መንገድ ለሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች የተለያዩ የተሣትፎ መድረኮች እንደሚያዘጋጁ ገልፀዋል፡፡
“ሕዝቡ ራሱ ያስፈፀመውና የውጤቱም ባለቤት የሆነበት” ያሉት ምርጫ በዓለም አቀፍ ደረጃ ቢታይ ከፍተኛ የሕዝብ ተሣትፎ የተስተዋለበትና ጥናት ሊደረግበት የሚገባ ክስተት መሆኑን ተናግረዋል።
የምርጫው ውጤት “ሕዝቡ ምን አለ?” ለሚል ጥያቄ አጥጋቢ ምላሽ ሰጥቷል፤ ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
ተጨማሪ ዝርዝር ዘገባዎች ተዘጋጅተው እንደተጠናቀቁ ይወጣሉ፡፡