በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

ኃይሌ ወጣ፤ ገብሬ ገባ


የዘንድሮው የኒውዮርክ ማራቶን አሸናፊ ገብረእግዚአብሔር ገብረማርያም ከኃይሌ ገብረሥላሴ ጀርባ የሚታየው ረጅሙና ግራጫ የራስ ሹራብ ያጠለቀው ነው፡፡ ፎቶግራፉ የተነሣው በክዊንስቦሮ ድልድይ ላይ ኃይሌ ውድድሩን አቋርጦ ከመውጣቱ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ነው፡፡
የዘንድሮው የኒውዮርክ ማራቶን አሸናፊ ገብረእግዚአብሔር ገብረማርያም ከኃይሌ ገብረሥላሴ ጀርባ የሚታየው ረጅሙና ግራጫ የራስ ሹራብ ያጠለቀው ነው፡፡ ፎቶግራፉ የተነሣው በክዊንስቦሮ ድልድይ ላይ ኃይሌ ውድድሩን አቋርጦ ከመውጣቱ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ነው፡፡

የረዥም ርቀት ሩጫው ንጉሥ ኢትዮጵያዊው አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ ዓለምአቀፍ የሩጫ ውድድሮችን ማቆሙን ይፋ አደረገ።

ኃይሌ ይህን ያስታወቀው ትናንት በኒው ዮርክ ማራቶን ያሸንፋል ተብሎ ሲጠበቅ ጉልበቱ ላይ በደረሰበት ህመም 16ኛው ማይል ላይ አቋርጦ ከወጣ በኋላ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው።

በረዥም ርቀት ሩጫ ውድድሮች በታሪክ ቀዳሚውን ሥፍራ እንደያዘ በስፋት የሚነገርለት የ 37 ዓመቱ አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ ላለፉት 18 ዓመታት የበላይነቱን ይዞ ከቆየ በኋላ ከአትሌቲክሱ ስፖርት ውድድሮች ራሡን ማግለሉን ሲናገር ዓለምን አስደንግጧል።

የዓለምአቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር ፕሬዘዳንት ላሚን ዲያክ ይህንኑ አስመልክተው ሲናገሩ «ይህ የስፖርት ጀግናና ብልህ አትሌት ጉልበቱ ላይ በደረሰበት ህመም ምክንያት ከዚህ ውሣኔ የመድረሱን ዜና የሰማሁት በታላቅ ኀዘን ነው» ብለዋል። በተከታታይ የዓለምና የኦሊምፒክ ሻምፒዮና እንዲሁም በማራቶን የዓለምን ክብረወሰን የያዘው ኃይሌ ገብረሥላሴ "ከስፖርተኛነቱም በላይ በዓለም ዙሪያ በሚሊዮኖች ዘንድ በደግነቱና በመልካም ምግባሩ ጭምር ይታወቃል" ሲሉም ላሚን ዲያክ አሞግሰውታል።

ለሁለት አሥርት ዓመታት ግድም እንዳንፀባረቀ የቆየው ኰከብ አትሌት ኃይሌ ከአትሌቲክሱ ስፖርት ውድድር ራሡን ለማግለል የወሰነው ከማናጀሩም ሆነ ሌላ ማንም ሰው ጋር ሳይማከር በራሱ መሆኑን እንባ እየተናነቀው አስረድቷል። በተጨማሪም ሌላ ሥራ ለመሥራትና ለወጣት አትሌቶች ዕድል ለመስጠት መሆኑን ገልጿል።

ኃይሌ ገብረሥላሴ አቋርጦ ቢወጣም ሌላ ጀግና ተወልዷል። በማራቶን ለመጀመሪያ ጊዜ የሮጠው አትሌት ገብረእግዚአብሔር ገብረማርያም በድል አጠናቋል። ከባለድሉ ገብሬ ገብረማርያም ጋር የተደረገውን አጭር ውይይትና ሙሉ ዘገባያዳምጡ።

XS
SM
MD
LG