በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

የጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሣለኝ ልዩ ቃለምልልስ ከቪኦኤ ጋር - ክፍል 2


ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ /ፎቶ ከፋይል የተወሰደ/
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ /ፎቶ ከፋይል የተወሰደ/

አቶ ኃይለማርያም ደሣለኝ ከቪኦኤው የአፍሪካ ቀንድ ኃላፊ ፒተር ሃይንላይን ጋር ባደረጉት ልዩ ቃለምልልስ ያነሷቸው ኢትዮጵያ ከኤርትራ፣ ከግብፅና ከሱዳን፣ ከቻይናና ከአሜሪካ ጋር ያሏትን ግንኙነቶች በዚህ ክፍል ውስጥ ያብራራሉ፡፡




please wait

No media source currently available

0:00 0:14:47 0:00
ቀጥተኛ መገናኛ

please wait

No media source currently available

0:00 0:27:54 0:00
ቀጥተኛ መገናኛ


የውጭ ጉዳዮች

በኤርትራ ጉዳይ

ቪኦኤ፡-

ለኢትዮጵያዊያን አነጋጋሪ ሆኖ የቆየውና የሚያሳስባቸው የውጪ ፖሊሲ ኤርትራን የሚመለከተው ነው። ይህ ለኢትዮጵያዊያን ቁልፍ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ በቅርቡ እርስዎ ከአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ሠላምታ በመለዋወጥ እንደተጨባበጡ ይነገራል፡፡ ስለዚያ እርግጠኛ አይደለሁም፤ ግን እውነት ከሆነ እርስዎ ይነግሩናል፤ ምናልባትም እንደገና ድርድር ለመጀመር እርምጃ አለ ይባላል። የኤርትራውን መሪ አነጋግረዋል? የሁለቱን አገሮች ግንኙነት ለማሻሻል የሚያስችል ሂደት ተጀምሯል?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡-

አመሠግናለሁ፤ ፒተር! ኤርትራን በሚመለከት ያለንን የውጭ ፖሊሲ አልለወጥንም፡፡ ፖሊሲያችን ጦርነቱን ተከትሎ የተቀረፀና ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት እየሠራ ያለ ፖሊሲ ነው፡፡ ያለአንዳች ቅድመ ሁኔታ መነጋገር እንፈልጋለን፡፡ ግንኙነታችንን ልናሻሽል የምንችልበት ብቸኛ መንገድ ንግግር ነው፡፡ ይህንንም ለኤርትራ መንግሥትና መሪዎች አሣውቀናል፡፡ ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት ይሆናል ብለን እየጠበቅን ነው፡፡ ወደፊትም በዚሁ እንቀጥላለን፡፡ የፖሊሲ ለውጥ የለንም፤ የፖሊሲውን አቅጣጫም ያወጣነው እኛው ነን፡፡ እኛ የምንለው ባለአምስት ነጥብ የሠላም ሃሣብ፣ የሠላም ስትራተጂ ነው፡፡ አሁንም ጠረጴዛ ላይ ያለ ነው፡፡ ግንኙነቶቻችንን ለማሻሻል ከኤርትራ መንግሥት ጋር በጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠን መነጋገር እንፈልጋለን፡፡ ስለዚህ አሁንም ሂደት ላይ ያለ ጉዳይ ነው፡፡

መጨባበጥን በተመለከተ ግን እኛ ኤርትራ ውስጥ ካሉ ሰዎች ጋር ችግር የለብንም፡፡ የአገዛዙ ችግር ነው፡፡ ተደርጎም ከሆነ ችግር የለውም፡፡ ግን አልተጨባበጥንም፡፡

አባይ፣ ግብፅና ሱዳን

ቪኦኤ፡-

ቀጥሎ የማቀርብልዎ ጥያቄ ግብፅን የሚመለከት ነው። እርስዎ እስካሁን የሠሩት በሥርዓተ-ትምህርት ዘርፍ ነው። ካልተሣሣትኩ በውኃ ምኅንድስና ዲግሪ አለዎት፤ ባለፉት ሁለት ዓመታት የአባይን ወንዝ በጋራ ስለመጠቀም ተወስቷል፡፡ ይህም በካይሮና በአዲስ አበባ መካከል ውጥረት ፈጥሯል ይባላል።
ባለፉት ጥቂት ቀናት የግብፅ ባለሥልጣናት ‘ኢትዮጵያ በውኃው አጠቃቀም ላይ አክራሪ አቋም ይዛለች’ ሲሉ በይፋም ባይሆን በሚስጥር መናገራቸው ተሰምቷል። በዚሁ ሰሞን ደግሞ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ1995 ዓ.ም በቀድሞው ፕሬዚደንት ሆስኒ ሙባረክ ላይ ግድያ በመሞከር ወንጀል ተፈርዶባቸው ኢትዮጵያ እሥር ቤቶች ውስጥ ስለሚገኙ ግብፃዊያን ጥያቄ መላኩን አስታውቋል። እነዚህ ሁሉ ግብፅ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት እንደገና የመመልከት አዝማሚያ ይጠቁማሉ፡፡ መጀመሪያ በእሥረኞቹ ጉዳይ ምን አስተያየት አለዎት? በተጨማሪ ደግሞ እርስዎ የሚመሩት መንግሥት በአባይ ወንዝ አጠቃቀም ላይ ከቀደሙት ጠቅላይ ሚኒስትር የተሻለ የሚባል አግባብና ለዘብተኛ አቋም ሊኖረው ይችላል?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡-

በቅድሚያ ፒተር፤ የአባይን፣ እንዲሁም የኢትዮጵያና የግብፅን ግንኙነት በሚመለከተው የውጭ ፖሊሲ ጉዳይ ላይ የውኃ መሃንዲስ መሆን አያስፈልግህም፡፡ ምክንያቱም ይህ ለማንም ኢትዮጵያዊ ግልፅ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ የአባይ ጉዳይ ለምዕት ዓመታት የቆየ ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መንግሥት ብቻ ሣይሆን በቀደሙ የኢትዮጵያ መንግሥታትም፣ እንዲያውም በግብፅም ከፈርዖን ዘመናት ጀምሮ ያለና እየቀጠለ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ይህ የአትዮጵያ ብቻም የሆነ ጉዳይ አይደለም፡፡ የሁሉም የአባይ ተፋሰስ ሃገሮች ጉዳይ ነው፡፡ የተፋሰሱ የራስጌም ሆነ የግርጌ ሃገሮች ጉዳይ ነው፡፡ ይህ የወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ዓለምአቀፍ ጉዳይም ነው፡፡

ይህንን በተመለከተ ከግርጌዎቹ ሃገሮች ከሱዳንና ከግብፅ ጋር ለመስማማት ልበ ሰፊ ሃገር ሆና ቆይታለች፡፡ ከግብፅ ጋር ብቻ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ውኃውን በጋራ የሚጠቀሙት እነርሱ ናቸው፡፡ አሁን ታዲያ በአባይ ተፋሰስ ውስጥ ያለን ሃገሮች የውኃው ተቀራራቢ ተጠቃሚ እንድንሆን የራስጌዎቹ ሃገሮች ስምምነት ላይ ደርሰናል፡፡

ይህ አስፈላጊ ጉዳይ ነው፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ለአባይ 86 ከመቶውን ውኃ የምታስገባ ሃገር ነች፡፡ ይህንን ውኃ ታዲያ ‘ኢትዮጵያ ለልማቷ ልታውለው አትችልም’ የምትል ከሆነ ይህ የቂል ሰው ስሌት ነው የሚሆነው፡፡ ካለበለዚያ ይህ እጅግ ቀላልና አመክኗዊ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ የግድ የውኃ ኢንጂነር መሆን የለብህም፡፡

ኢትዮጵያ ሁልጊዜ በግርጌዎቹ ሃገሮች፣ በሱዳንና በግብፅ ላይ አንዳችም የጎላ ጉዳት ሳይደርስ ውኃውን መጠቀም ትፈልጋለች፡፡ በቴክኒክ ደረጃም እነዚያን የግርጌ ሃገሮች ሳንጎዳ የራስጌዎቹ ሃገሮች ተጠቃሚ ልንሆን እንችላለን፡፡ ይህ መፍትሔ እስካለን ድረስ ለምን አንተባበርም? በመሆኑም ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ለኃይል ማመንጫ የሚውሉ ግድቦችን መገንባት ጀመረች፡፡ ይህ ደግሞ ውኃውን ወደ ሌላ አቅጣጫ የሚወስደው ወይም የሚያስቀረው አይደለም፡፡
በተጨማሪም በሱዳን፣ በግብፅና በሁሉም የምሥራቅ አፍሪካ ሃገሮች ውስጥ ያለውን ኢኮኖሚ ለማሳደግም አስተዋፅዖ ያበረክታል፡፡ በመሆኑም ይህ ሁሉም አሸናፊ፣ ሁሉም ተጠቃሚ የሚሆንበትና ነገሮችን በትብብር መሥራት የሚቻልበት መስክ በመሆኑ ሁላችንም ወደ ትብብሩ መምጣት አለብን፡፡
በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ በጣም ግልፅ የሆነና መታየት የሚችል ሃሣብ ለግብፅና ለሱዳን አቅርባ የሱዳን፣ የግብፅ፣ የኢትዮጵያ ባለሙያዎች ያሉበትን አንድ ቡድን ለማቋቋም ተስማምተናል፡፡

በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ምክንያት በግብፅና በሱዳን ላይ የሚደርስ ጉዳት መኖር አለመኖሩን የሚከታተሉ ዓለምአቀፍ ታዛቢዎችም ተካትተዋል፡፡ ይህ የኢትዮጵያና ያለፉ ጠቅላይ ሚኒስትሯ ሃሣብ የሚያመለክተው አብረን የመሥራትና የማደግ መንገድን ለመሻት ያለንን ብርቱ ፍላጎት ነው፡፡

አባይ፣ አብረን ለማደግ አብረን መሥራት የምንችልበት ብቸኛው ጉዳይ አይደለም፡፡ አባይ፣ ለዲፕሎማሲያችንና ለምጣኔ ኃብት መቀናጀት መሠረታዊና ማዕከላዊ ጉዳይ ነው፡፡ ሆኖም ግን ብቸኛው መንገድ አይደለም፡፡ መናገድ እንችላለን፤ አንዱ በሌላው ሃገር ውስጥ ኢንቨስት ማድረግ ይችላል፤ በሕዝቦች ግንኙቶች ላይ መሥራት እንችላለን፡፡ ግንኙነቶቻችንን ከግብፅና ከሱዳን ጋር በብዙ መንገዶች ማጠናከር እንችላለን፡፡

ችግሩ የቀደመው የግብፅ መንግሥት ነበር፡፡ የአሁኑ መንግሥት ምን እንደሚያደርግ ሰንብተን እናየዋለን፡፡ ያለፈው ግን የአባይን ጉዳይ የሚያየውና የያዘውም እንደፀጥታ፣ እንደደህንነት ጉዳይ ነበር፡፡ የውጭ ዲፕሎማሲ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም ጉዳይ አልነበረም፡፡ የአባይን ጉዳይ የያዘውም የደህንነት ኃላፊው ነበር፡፡

አሁን እየተሰሙ ያሉ ጭምጭምታዎች አሉ፡፡ ‘የደህንነት ጉዳይ ነው፤ ግብፅ እንደደህንነት ጉዳይ ነው የያዘችው’ የሚሉ፡፡ ይሁን እንጂ እኔ የአሁኑን መንግሥት አቋም አሁን ልነግርህ አልችልም፡፡ የሽግግሩ መንግሥት ከእኛ ጋር ቆሞ ነበር፡፡ አንዳንዶቹ መሪዎችም የአዲሱ መንግሥት አባል ናቸው፡፡ በቅርብ እየተከታተልነው ነው፡፡ ምክንቱም በዚህ ጉዳይ ላይ የሠሩ ባሉት ቡድኖች ላይ የተፈጠረ ችግር የለም፡፡ አሁን ያለው የተሣካና የተጣጣመ የሥራ ግንኙነት ነው፡፡

የእኛ ጉዳይ ግን አባይ ላለመተማመን ምክንያት መሆን የለበትም የሚል ነው፡፡ አብሮ የመሥራት፣ የመተማመንና የመተባበር፣ የጋራ ጥቅም፣ አብሮ የማደግና ሁላችንም አሸናፊ የምንሆንበት መፍትሔ ጉዳይ እንዲሆን ነው የምንፈልገው፡፡ ይህ ደግሞ ይቻላል፡፡ ለዚያም እንሠራለን፡፡ መጋጨት አያስፈልገንም፡፡ ስድስት ሺህ ሜጋዋት ኃይል ካመነጨን በደጋማው መልክአምድራዊ አቀማመጧ ምክንያት ኢትዮጵያ ከተጎናፀፈችው ፀጋ የሚወጣውን የውኃ ኃይል ማስተባበር ማቀናበርና ማገናኘት፣ ከዚያም ሁላችንም ተጠቃሚ መሆን እንችላለን፡፡ ይህ ነው የሚፈለገው፡፡

ሱዳንን ብትመለከት፣ በዚህ ግድብ ምክንያት ሱዳን የተገራ ውኃ ማግኘት ትችላለች፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ስትነፃፀር ሱዳን ለግብርና ልታውል የምትችለው በቂ ስፋት ያለው መሬት አላት፡፡ ይህም በራሱ ፀጋ ነው፡፡ ሱዳን ውስጥ በመስኖ የሚለማ ግብርና ካለ፤ ከውጤቱ ሁላችንም ተጠቃሚ እንሆናለን ማለት ነው፡፡ በግብፅም እንዲሁ፡፡ በመሆኑም አብሮ የመሥሪያ እንጂ የፀጥታና የደህንነት ጉዳይ አድርገን ልንይዘው አይገባም፡፡ የአባይ ምሥራቅ ተፋሰስ ሃገሮች፤ የኢትዮጵያ፣ የግብፅና የሱዳን ሕዝቦች በጋራ የምንለማበት ጉዳይ ነው ማድረግ ያለብን፡፡ አሁን በግምት መመራት አንፈልግም፤ ለጊዜው አሁን ባለው የግብፅ መንግሥት ዘንድ የፖሊሲ ለውጥ አላየንም፡፡

ቪኦኤ፡-

ግብፃዊያን እሥረኞቹን አስመልክቶ ስላቀረቡት ጥያቄስ መልስዎ ምንድነው?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡-

ይህ ባለፈው መንግሥት የተዘጋ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ አየህ! የሽብር ፈጠራ አድራጎቶች በማንኛውም መልክ ቢሆን አይመከሩም፤ ተቀባይነትም የላቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ፍርድ ቤት የቀድሞውን የግብፅ ፕሬዚዳንት ለመግደል በሞከሩት ላይ የሞት ቅጣት ፈርዶባቸዋል፡፡ ይህ ባለፈው መንግሥት የተዘጋ ጉዳይ በመሆኑ በዚህ ወቅት የምንመለስበት ምክንያት የለም፡፡

ርዕዮተ-ዓለም፣ ቻይና፣ አሜሪካና ሌሎች

ቪኦኤ፡-

የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ብዙውን ጊዜ ቻይናን “በኢኮኖሚ እምርታ እያሣየች ያለች” እያሉ በአድናቆት ይገልፁ ነበር። ምዕራባዊያን አገሮችን ደግሞ እየወደቁ ያሉ ኃይሎች ሲሉ በመግለፅ ነቀፋ ያሰሙ ነበር። ኢህአዴግ ከቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ ጋር ስላለው ቅርበት በሰፊው አስታውቀዋል። ምዕራባዊያን ኢኮኖሚአቸው እየወደቀ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በርዕዮተ-ዓለም ቅርበት ካላትና ታዳጊ የኢኮኖሚ ኃይል እየተባለች ካለችው ቻይና ጋር ግንኙነቷን ማጠናከር ይሻላታል ብለው ያምናሉ?

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም፡-

ከሁሉም በፊት ከሃገሮች ጋር ያሉን ግንኙነቶች የሚመሠረቱት በርዕዮተ-ዓለም ጉዳይ ላይ አይደለም፡፡ ከግንኙነቶቹ በምናገኛቸው ጥቅሞች ላይ የተመሠረቱ ናቸው፡፡ እንደዚሁ ዓይነት ጥያቄ ከዚህ በፊትም ጠይቀኸኝ የመለስኩልህ በተመሣሣይ መንገድ ነው፡፡ በመሆኑም ከዩናይትድ ስቴትስም፣ ከቻይናም ጋር ያሉን ስትራተጂካዊ ግንኙነቶች ናቸው፡፡

ይህ ስትራተጂካዊ ግንኙነት ተነጥሎ የተወሰደን ሃገር ባነሣህ ቁጥር የራሱ የሆኑ ደርዞች አሉት፡፡ ዩናይትድ ስቴትስ ከኢትዮጵያ ጋር በምጣኔ ኃብት ልማት በኩል በጣም የቅርብ አጋር ነች፤ በተለይ ግብርናን፣ የጤና ዘርፍና ሰብዓዊ ድጋፍን በመሣሰሉ ጉዳዮች ላይ፡፡ ይህ ግዙፍ ድጋፍ ነው፡፡ ለዚህ ድጋፍ ደግሞ የዩናይትድ ስቴትስን ሕዝብና መንግሥት እናመሠግናለን፡፡ በአካባቢያችንና በዓለም አቀፍ ደረጃም ሠላምና ፀጥታን በሚመለከት ስትራተጂያዊ ወዳጆች ነን፡፡ የሃያዎቹን ከበርቴ ሃገሮች፣ የስምንቱን ሃያላን ሃገሮች ቡድኖች በመሣሰሉት መድረኮች ላይ ፍትሕ የሰፈነበት፣ ተመጣጣኝ ክፍፍል ያለበት ዓለም እንዲኖር፣ በአየር ንብረት ለውጥና ሌሎችም ጉዳዮችን በተመለከተ አብረን እንሠራለን፡፡ በመሆኑም ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ባለን ግንኙነት ዓለምአቀፍ፣ አካባቢያዊና የሁለታችን የሆኑ የጋራ ሥራዎች አሉን፡፡

ሁለተኛ - ቻይና፡፡ ቻይና ስትራተጂያዊ ወዳጃችን ነች፡፡ በመሠረተ-ልማት፣ በመዋዕለ-ነዋይ ታግዘናለች፡፡ ብዙ የውጭ ቀጥተኛ መዋዕለ-ነዋይ ከቻይና ወደ ኢትዮጵያ እየገባ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ከዩናይትድ ስቴትስና ከአውሮፓ የሚመጣውም የውጭ ቀጥተኛ መዋዕለ-ነዋይ ፍሰት ጨምሯል፡፡ ይህንን በተመለከተ እኛ ለርዕዮተ-ዓለም ጨርሶ ዐይን የለንም፡፡ ከሃገሮች ጋር ግንኙነቶችን እንድንመሠርት የሚያደርጉን ለሕዝባችን የሚጠቅሙ፣ ለሃገራችን የሚጠቅሙና የብሔራዊ ጥቅም ጉዳዮቻችን ናቸው፡፡ ዲፕሎማሲያችን ግልፅ ነው፡፡ የውጭ ግንኙቶታችን ድብቅ ነገር የላቸውም፤ ዘልቀው የሚታዩ ናቸው፡፡ መሠረታቸው ርዕዮተ-ዓለም አይደለም፡፡

ፓርቲያችን ከቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ ጋር የቅርብ ትሥሥር አለው፡፡ ምክንያቱም የቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ እያከናወነ ካለው ልንማራቸው የምንችላቸው አካባቢዎች አሉ፡፡ በአጭሩ እኛ ያለን ፖሊሲ ሕዝብን መሠረት ያደረገ እና ልማትን ማዕከል ያደረገ ነው፡፡ በዚህ አካባቢ እታች ወርዶ በመሥራት የቻይና ኮምዩኒስት ፓርቲ ልምድ አለው፡፡ በመሆኑም እንዲህ ዓይነቱን አያያዝ ከቻይና እንማራለን፡፡ ይህ ማለት ግን ርዕዮተ-ዓለማችን ከቻይናው ጋር ተመሣሣይ ነው ማለት አይደለም፡፡ ከሁሉም ሃገር፣ ከሁሉም ፓርቲ የምትማራቸው የተሻሉ ልምዶች አሉ፡፡ እንደምታውቀው እኛ ግራ ዘመም ፓርቲ ነን፡፡ እኛ ከቻይና ጋር ብቻ ሳይሆን ከጀርመኑ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ ጋርም በዚሁ ግራ ዘመም አመለካከታችን ምክንያት እንሠራለን፡፡ ከኤኤንሲ ጋር እንሠራለን፡፡ ከሌሎችም የአውሮፓ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲዎች ጋር እንሠራለን፡፡ ከእንግሊዙ ሌበር ፓርቲ ጋርም እንሠራለን፡፡ ከአንዱ ወይም ከሌላው ትማራለህ፡፡

እኛ ኢትዮጵያ ውስጥ የራሣችን ርዕዮተ-ዓለም እንዳለን ነው የሚሰማን፡፡ የራሣችን ነው፤ ብሔራዊ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከአንዳንዶች ወይም ከሌሎች ጋር ተመሣሣይ ጎኖች ሊኖሩት ይችላሉ፡፡ ለፓርቲያችን ሚጠቅሙ ሆነው የምናዘምባቸው ጉዳዮች ካሉ እንማርባቸዋለን፤ ልምድ እንቀስምባቸዋለን፡፡ እንዳለ እንወስዳቸዋለን ማለት ሳይሆን ከራሣችን ሁኔታ ጋር ማዛመድ የምንችልበትን መንገድ እንፈልጋለን፡፡ በሃገር ደረጃ፣ በፓርቲው የውስጥ አሠራሮች ውስጥ፣ በዓለም ውስጥ ካሉ ሶሻሊስት ዓለምአቀፍ አባል ከሆኑ ፓርቲዎች ሁሉ ጋር መሥራት እንፈልጋለን፡፡ በአውሮፓ፣ በዩናይትድ ስቴትስ፣ በቻይናና በሌሎችም የዓለማችን አካባቢዎች አሉ፡፡
/ተፈፀመ/
XS
SM
MD
LG